Monday, May 23, 2011

የኢንዱስትሪ ልማት ተስፋዎች

የመሀከለኛው ክብ ወደ ጐን ለሁለት የተከፈለ ነው። ከታችኛው ክፋይ ባለው ቦታ መዶሻ፣ መሰላል፣ የልብስ መስፊያ ሲንጀር፣ ሌሎች መሣሪያዎች አረንጓዴ ቀለም መደብ ጐልተው ይታያሉ። ከላይኛው ወገን የቢጫ ቀለም መደብ ላይ የኢንዱስትሪ ምልክት በደማቁ ሰፍሯል – ሰባት ዓመታትን ያስቆጠረው የልማት ተጓዥ የጥቃቅንና አነስተኛ ልማት ኤጀንሲ አርማ።አረንጓዴ ቀለም የልምላሜ፣ ቢጫው ደግሞ የብሩህ ተስፋ ምልክት ስለመሆናቸው እርግጥ ነው።
በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የመሰብሰቢያ አዳራሽ ኢትዮጵያውያን በሚወዱት ሰንደቅ ዓላማቸው ላይ ያሉ ሁለት የመጀመሪያ ቀለሞችን ወክለው የለበሱ በርካታ የልማት አርበኞች በየወንበራቸው ተቀምጠዋል። ባላጋራቸውን ታግለው የረቱ ባለድል በመሆናቸው የፊታቸው ገፅታ ፈክቷል። ድህነት እንደሚሸነፍ በተግባር ያረጋገጡ የመሆናቸው እውነት ፊታቸው ይናገራል። በተለይ ቢጫውን ጋዋን የለበሱ ኢንተርፕራይዞች ከፊታቸው የቆመውን ችግር በማለፍ፤ መሰላሉን በብዙ ውጣ ውረድ በመውጣት ከግባቸው የደረሱ ናቸው። በዕለቱ ተመርቀው ወደ መካከለኛ ኢንዱስትሪ መሸጋገራቸውን የሚያረጋግጡ የልማት ጀግኖች ናቸው። በነጭ ቲ ሸርት ላይ አረንጓዴውን መቀነት ወደ ጐን ያጠለቁትም ቢሆኑ ከኢንተርፕራይዝነት ወደ ሞዴል ኢንተርፕራይዝነት የተሸጋገሩ በመሆናቸው በደስታ ፈክተዋል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ለበርካታ የጥቃቅንና አነስተኛ አንቀሳቃሶች የተለያዩ ድጋፎችን በማድረጉ በሺ የሚቆጠሩ የከተማ ነዋሪዎች በዘርፉ እንዲታቀፉ ማድረጉን መረጃዎች ያመለክታሉ። ከደቂቃ ሙት ውስጥ 250 ኢንተርፕራይዞች ወደ መካከለኛ ኢንዱስትሪ መሸጋገር የሚችሉበት ደረጃ ላይም መድረሳቸውን አረጋግጠዋል።
ከእነዚህ መካከል የዮሽ ኮንስትራክሽን ኢንተርፕራይዝ አንዱ ነው። ሥራ አስኪያጁ አቶ ዮሐንስ ይግለጡ እንደሚናገሩት የኢንተርፕራይዙ ካፒታል አምስት ሚሊዮን ደርሷል።
አቶ ዮሐንሰ እንደተናገሩት፤ ኩባንያቸውን ያቋቋሙት በ2000 ዓ.ም ነው። የተሰማሩበት ዘርፍ ኮንስትራክሽን ቴራዞንና የግንባታ ሥራዎች ነው። የቴራዞን ማሽኖችን እየሠሩም ለሌሎች ኢንተርፕራይዞችና ድርጅቶች ይሸጣሉ።
በጥቃቅንና አነስተኛ ተቋም ጀምረው ወደ መካከለኛ ኢንዱስትሪ በመሸጋገራቸው እድለኛ መሆናቸውን ይናገራሉ። አቶ ዮሐንስ እንደሚሉት፤ መንግሥት የተለያዩ ድጋፎችን አድርጐላቸዋል። በድጋፉም በእጅጉ ደስተኛ ናቸው። ከአዲስ ብድር ቁጠባ በተለያየ ጊዜ ብድር መውሰዳቸውንም አውግተውናል።
በተቋቋሙበት ወቅት «በምን ዓይነት ሥራ ብንሰማራ ውጤታማ መሆን እንችላለን ብለን በማሰባችን ለዛሬው ውጤት አብቅቶናል እድለኞች ነን» ይላሉ ሥራ አስኪያጁ። በወቅቱ በመረጡት የቴራዞን ዘርፍ ማንም ኢንተርፕራይዝ እንዳልነበር ያስታውሳሉ። እንዲያውም ሥራውን የሚሠሩ በቁጥር ሦስት አራት የሆኑ የመንግሥት ትልልቅ ተቋማት ብቻ እንደሆኑም ይናገራሉ።
እንደ ሥራ አስኪያጁ ገለፃ፣ ሥራውን በሚጀምሩበት ወቅት ብዙ ሰዎች ገበያ አታገኙም የሚል አስተያየት ይሠጧቸው ነበር። በርግጥ በወቅቱ የገበያ ሁኔታ ፈታኝ ሆኖባቸዋል። በተጨማሪም 'በጥቃቅንና አነስተኛ ሥራ እንዴት ይደፈራል?' ያሏቸው ወገኖችም አሉ።
«ያም ሆኖ መንግሥት የገበያውን ስጋት ትስስር በመፍጠር ያቃለለው ሲሆን፤ በዚህም የተሻለ ውጤት በማምጣታቸው ቤቶች ልማት ላይ ጥሩ ሥራዎችን አከናውነዋል። ኢንተርፕራይዛቸው በራሱ ካፒታል የድንጋይ 'ክርኤቸር ሳይት' ተጫርቶ ገዝቷል» ብለዋል አቶ ዮሐንስ።
ኢንተርፕራይዛቸው ወደ መካከለኛ ኢንዱስትሪ በመሸጋገሩ የሚያከናውናቸው ሰፋፊ ሥራዎች እንዳሉ ይጠቁማሉ። ለኤጀንሲው «የ20 ሚሊዮን 770 ሺ ብር ፕሮጀክት» አስጠንተው አቅርበዋል።
ቀደም ሲል በሚሠራው ሥራ ኢንተርፕራይዛቸው 47 ያህል ለሚሆኑ ሰዎች የሥራ ዕድል መፍጠሩን የተናገሩት ሥራ አስኪያጁ፤ ቴራዞን ማሽኖችን በክልል ደረጃም እየታዘዙ ይሰሩ እንደነበር ነው ያብራሩት።
አካ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር የተቋቋመው በ1997ዓ. ም ነው። የተሰማራበት የሥራ ዘርፍም በእንጨትና ብረታ ብረት ነው። የኢንተርፕራይዙ ባለቤትና ሥራ አስኪያጅ አቶ አብዲላሀዲ ዓሊ በበኩላቸው በመመረቃቸው ከፍተኛ ደስታ እንደተሰማቸው ይገልፃሉ።
በአሁኑ ወቅት ወደ መካከለኛ ኢንዱስትሪ ሊሸጋገሩ የቻሉት ከአምስት ሚሊዮን ብር በላይ ካፒታል በማድረሳቸው እንደሆነ የሚገልጹት አቶ አብዱላሀዲ፤ በኢንተርፕራይዛቸው ወደ 14 የሚሆኑ ሠራተኞች የሥራ ዕድል እንዳገኙ ይገልፃሉ።
አቶ አብዱላሀዲ እንደሚናገሩት፤ ሽግግሩ የሥራንም ትጋት የሚጠይቅ ነው። ወደፊት ሊሠሩ ያቀዱት የፓስታ፣ ማካሮኒ፣ ዱቄትና ብስኩት ፋብሪካ በመገንባት ነው። ይህም ለብዙዎች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ይችላል። ለዚህም የ13 ሚሊዮን ብር ፕሮጀክት ቀርፀው ለኤጀንሲው አስገብተዋል። ሁሉ ነገር ከተመቻቸላቸው አንዲትም ቀን ሳያሳልፉ ሥራ ለመጀመር ያላቸውን ብቃት በልበ ሙሉነት ይናገራሉ። «ሁሉም ሰው ያለመታከት በትጋት ሥራውን የሚያከናውን ከሆነ በሚያጋጥመው ጥቃቅን መሰናክል አይበገርም» የሚል እምነት አላቸው።
በ2001 ዓ.ም የተቋቋመው የጋላክሲ ኮንስትራክሽን ኢንተርፕራይዝ የተሰማራው በኮንስትራክሽኑ ዘርፍ መሆኑን የማኅበሩ ሊቀ መንበር አቶ አወቀ ጐዳና ይገልፃሉ።
እንደ አቶ አወቀ ገለፃ፤ ኢንተርፕራይዙ ያስመዘገበው አንድ ነጥብ አምስት ሚሊዮን ብር ካፒታል ነው። አስራ አንድ አባላት አሉት። ከአባላቱ ውጪ በተለያዩ ኮንስትራክሽን ሥራ ውስጥ የሚሠሩ 106 የጉልበት ሠራተኞችና ሦስት ቋሚ ተቀጣሪዎች አሉት።
ቀደም ባሉ ጊዜያት ሥራቸውን ሲያከናወኑ በርካታ ማነቆዎች አጋጥሟቸው እንደነበር አቶ አወቀ ያስታውሳሉ። ሰው በተሰማራበት ሥራ በቁርጠኝነት የሚሠራ ከሆነ የሚያጋጥመውን እንቅፋት በትዕግስት ማለፍ ይችላል ይላሉ። ኢንተርፕራይዞችም ሆኑ ሞዴል ኢንተርፕራይዞች ሊያጋጥማቸው ለሚችል ማንኛውም ፈተና እጅ መስጠት እንደሌለባቸው በመግለፅ።
«ጥቂት የማይባሉ ፈተናዎችን አልፌ በመሥራቴ በጣም ደስተኛ ነን» ያሉት አቶ አወቀ፤ መንግሥት 'ሁሌም ከጐናችሁ ነኝ' ከማለትም ሌላ በተግባር በርካታ ድጋፎችን በማድረጉ አሁንም የስኬት ጉዞዬን አጠናክራለሁ ሲሉ ሀሳባቸውን አጋርተውናል።
ቀደም ሲል ይሠሩ የነበረበትን ዘርፍ በመለወጥ ወደ ግብርናው ለመግባት የ14 ሚሊዮን ብር ፕሮጀክት መንደፋቸውን ገልጸው፤ በተለይ ከብት አደልበው ወደ ውጭ ሀገር ለመላክ በተጓዳኝም ሌሎች ሥራዎችን ለመሥራት መዘጋጀታቸውን ነው ያብራሩት።
እንደ እርሳቸው አነጋገር የመመረቃቸው ፋይዳ ብዙ ነው። ጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዝ ተቋም ከተወሰነ ጣሪያ በላይ ለመንቀሳቀስ ሕጉ አይፈቅድም። አሁን ግን ከምረቃው በኋላ በተሰጣቸው እውቅና የተሻለ ነገር ለመሥራት ያስችላቸዋል። «ኢንቨስትመንት ውስጥ መግባት በራሱ ቀላል ነገር አይደለም። ይሁንና ያለፈውን ውጣ ውረድ ያለፍኩበትን ጥበብና ትጋት እንደ ተሞክሮ በመውሰድ በቀጣይም የተሻለ ነገር ለመሥራት በግንባር ቀደምትነት ለመንቀሳቀስ ዝግጁ ነን» ብለዋል።
ራዕይ ቅዱስ ሚካኤል ኮንስትራክሽን ኢንተርፕራይዝ ከአንድ ነጥብ ስድስት ሚሊዮን ብር በላይ ካፒታል እንዳለው የሚናገሩት ሊቀመንበሩ አቶ ሰለሞን ንጉሴ ናቸው። በ1997 ዓ.ም የተቋቋመው ኢንተርፕራይዛቸው የተሰማራበት ዘርፍ በእንጨትና ብረታ ብረታ እንደሆነ አመልክተው፤ የሚያመርተውም እንደ ብሎኬትና ፕሪካስት ዓይነት ምርቶች እንደሆነ ጠቁመዋል።
ሥራውን ሲጀምሩ በሁለት ሺ ብር እንደሆነ የሚያስታውሱት ሊቀመንበሩ፤ በአሁኑ ወቅት ከ30 የማያንሱ ሠራተኞች የሥራ አድል እንደተፈጠረላቸው ይናገራሉ። ከእነዚህ መካከል አምስቱ ቋሚ ሠራተኞች ናቸው ብለዋል።
ሊቀመንበሩ የወደፊት እቅዳቸውን ሲገልጹ ያሉበትን ዘርፍ በማጠናከር ዝግጅታቸውን አጠናቀዋል። በተለይ ትልልቅ ፋብሪካዎችን ለመገንባት አቅደዋል።
«ማንኛውም ሥራ ፈላጊ ሰው ሥራ ሳያማርጥ መሥራት አለበት» የሚል እምነት እንዳላቸው አቶ ሰለሞን ገልጸው፤ ሥራ ማማረጥ ግን የቀረ አሊያም የኋላቀርነት መገለጫ አድርገው እንደሚወስዱ ነው የተናገሩት።
በዕለቱ ወደ መካከለኛ ኢንዱስትሪ የተሸጋገሩትን ኢንተርፕራይዞች የመረቋቸው የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ ሲሆኑ፤ በዘርፉ የተማረ የሰው ኃይል በተለይም ከከፍተኛ የትምህርት ተቋም ተመርቀው የሚወጡ ወጣቶች እንዲሁም ሴቶች ሊሳተፉበት ይገባል ሲሉ ነው ያስገነዘቡት።
ለዘርፉ የተሻለ አመለካከት ያላቸው የልማት ጉዞአቸው ስኬታማ ሆኖ እነሆ ሰሞኑን ለመሸለም እና ለመመረቅ በቅተዋል፡፡ ከአዲስ አበባ አነስተኛና ጥቃቅንና ኢንተርፕራዝ ልማት ኤጀንሲው በተገኘ መረጃ መሠረት ከ20 ሺ ጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዝ መካከል 400 ያህሉ ከ200 ሺ ብር በላይ ካፒታል በማስመዝገባቸው የተሸለሙ ሲሆን፤ ከአንድ ነጥብ አምስት ሚሊዮን እስከ 20 ሚሊዮን ብር ካፒታል ያስመዘገቡ ደግሞ ተመርቀው ወደ መካከለኛ ኢንዱስትሪ በመሸጋገራቸው ልማታዊ ባለ ሀብት ተፈጥሯል።

source..http://www.ethpress.gov.et/ethpress/main/news.php?newsLocation=home&newsInstruction=headline&newsId=2680

No comments:

Ethiopian can not afford a prolonged war.

Ethiopian can not afford a prolonged war. Ethiopia as the poorest country in the world is dependent on aid. A prolonged war simply depletes ...